ማህበሩ ከሞኤንኮ ኢትዮጵያ የገዛቸውን ትራክተሮች እና ለመንገድ ሥራ አገልግሎት የሚውሉ ማሽኖችን በዛሬው ዕለት በወላይታ ጉተራ ሆቴል፣ ቱሪዝምና ስልጠና ማዕከል ላይ በመገኘት ተረክቧል ።
ማህበሩ ከምስረታው አንስቶ በዘላቂ ኑሮ ማሻሻል ላይ ትኩረቱን በማድረግ በርካቶችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉ አይዘነጋም ።
በግብርናው ዘርፍ ከአርሶ አደሩ ጎን በመሆን ከመስራት ባለፈ ግብርናን በማዘመን ኋላ ቀር አሰራሮችን በመተው ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀም አስፈላጊ በመሆኑ እና ለላቀ ምርታማነት ይረዳው ዘንድ እነዝህን ማሽኖች በዛሬው ዕለት ተረክቧል ።
ማህበሩ ከወላይታ ዞን እና ከሶዶ ከተማ አስተዳደር ባገኘው የገንዘብ ድጋፍ እና በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፍይናንስ አቅራቢነት በሦስት መቶ ሚሊዮን ብር ወጪ ለእርሻ እና ለመንገድ ሥራ የሚውሉ በቁጥር 18 ትራክቶችን፣ አንድ ባክሎድር እና ግሬደር ግዢ ፈፅሟል ።
በርክብክብ መርሃግብሩ ላይ የተገኙት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅ/ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ገ/መስቀል ጫላ ይህችን ቀን ”ለወላይታ የታሪክ እጥፋት ቀን” በማለት የገለፁ ሲሆን ከዚህ ቀደምም በህዝብ ተሳትፎ የማይደፈሩ ልማቶችን በመስራት የሚታወቅው የወላይታ ህዝብ ዛሬም ያንን ታሪክ ደግሟል ብለዋል።
የዛሬው ለወላይታ ህዝብ የማደግ ምልክት ነውና ይህን የዛሬውን ድጋፍ በመጠቀም ለላቀ ውጤታማነት እንዲሰራ እና የወላይታ ህዝብ ተጠቃሚ እንዲሆን ለማድረግ እንደ ልማት ማህበሩ ቦርድ ሰብሳቢ ቃል እገባለውም ብለዋል።
የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ረ/ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ በበኩላቸው የወላይታ ልማት ማህበር ከዳግም ምስረታው ጀምሮ ከመንግሥት ጎን በመሆን በርካታ ልማቶችን በመስራት የህዝቡ አለኝታነቱን ሲያሳይ የቆየ ማህበር ነው በማለት ለዘመናት በተለምዶ አስተራረስ የቆዩ አርሶአደሮችን በማዘመን ለተሻለ ምርታማነት የሚተጋበት ጊዜ ላይ በመሆኑ እነዝህ ማሽኖች ተገዝተዋል እና ከዚህ በኋላም ማህበሩን ለመደገፍ በምናደርገው እንቅስቃሴ ሁሉ ህዝቡ ከጎናችን መቆም አለበት ሲሉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል ።
የወላይታ ልማት ማህበር ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ አሰፋ ናና በተገዙት ማሽኖች ለወላይታ ህዝብ የሚታይ ልማት በመስራት ወላይታን ለማበልፀግ ይበልጥ እንደሚሰራ ገልፀው ስለተደረገው ድጋፍም ምስጋና አቅርበዋል።
በርክክቡ የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪና የማህበሩ ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ገ/መስቀል ጫላ፣ ምክትል ር/መስተዳድር ማዕረግ የዲላ ክላስተር አስተባባሪ እና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር መሪሁን ፍቅሩ፣ የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪና የልማት ማህበሩ የበላይ ጠበቃ ረ/ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ፣ የወላይታ ሶዶ ከተማ ከንቲባ ወ/ሮ እታገኝ ኃ/ማርያም፣ የዞኑ ብልፅግና ፓርቲ ቅ/ጽ/ቤት ኃላፊ ዶ/ር አማረ አቦታን ጨምሮ የዞኑና የወላይታ ሶዶ ከተማ አስተባባሪ አካላትና አጠቃላይ አመራር እና ሌሎች የልማት ማህበሩ ቦርድ አመራሮች ተገኝተዋል።








